እሳት ወይ አበባ
ሌ ት ከዋክብቱ እንደፀደይ
አጥለቅልቆን በቀይ አደይ
ሰማዩ ሥጋጃ አጥልቆ
ተሽለምልሞ አንጸባርቆ
ፈክቶ፥ አሸብርቆ ደምቆ
በአዝመራ፥ በአጥቢያ ዐፀድ ሰፍኖ
የዓደይ አዝርዕት ተከሽኖ
በዕንቁጣጣሽ ሰብል ታጥኖ
ኢዮሃ አበባዬ ሆኖ፥
ጨረቃዋ ከቆባዋ፥ ከሽልምልሚት እምቡጧ
ጧ ብላ ከሰንኮፈንዋ፥ ተንዠርግጎ የእንኮይ ቡጧ፥
ድንግል ጽጌ-ረዳ ፈልቃ
ፍልቅልቂት ድምቡል ቦቃ …
ተንሠራፍታ የአበባ ጮርቃ፥
ታድያን ብሌኑ የጠጠረ
ባሕረ-ሃሳቡ የከረረ
የውበት ዓይኑ የታወረ
ልበ-ሕሊናው የሰለለ
አይ፥ አበባ አይደለም አለ፤
አይ፥ እሳት አይደለም አለ፤
ያልታደለ። …
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ፥ እሳት አደል ብሎ ካደ
እቶን ባይኑ እየነደደ።
ከዋክብቱ እንደ ችቦ
በነበልባል ወርቀ ዘቦ
ከፅንፍ ፅንፍ አውለብልቦ
ደመራው እየተመመ
እየፋመ እየጋመ
ደመና እንደንዳድ ሲነድ
መንጸባርቅ ሰደድ ሲወርድ፥
በራሪ ኮከብ ተኩሶ
በአድማሳት እሳት ለኩሶ…
ይኸ እንደኔና እንዳንቺው፥ የውበት ዓይኑ የሰለለ
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ፥ እሳት እኮ አይደለም አለ፥
ያልታደለ። …
… ይቅር ብቻ አንናገርም፥
እኔና አንቺ አንወያይም፤
ለውይይት አልታደልንም
እንዲያው ዝም፥ እንዲያው ዝም … ዝም።
አበባ አንሆን ወይ እሳት
ተጠምደን በምኞት ቅጣት
ሰመመን ባጫረው መዓት
ዕድሜአችንን እንዳማጥናት፤ …
እሳት አንሆን ወይ አበባ
በሕቅ እንቅ ስንባባ
ባከነች ልጅነታችን፥ እየቃተትን ስናነባ
ሳንፈጠር በሞትንባት
ሳናብብ በረገፍንባት
ሳንጠና ባረጀንባት
አበባ ወይንም እሳት፥ መሆኑን ብቻ አጣንባት።
“— እሳት ወይ አበባ | ከጸጋዬ ገብረ መድኅን | 1960/1999 ዓ.ም ታተመ | ገጽ 152-154
ሌ ት ከዋክብቱ እንደፀደይ
አጥለቅልቆን በቀይ አደይ
ሰማዩ ሥጋጃ አጥልቆ
ተሽለምልሞ አንጸባርቆ
ፈክቶ፥ አሸብርቆ ደምቆ
በአዝመራ፥ በአጥቢያ ዐፀድ ሰፍኖ
የዓደይ አዝርዕት ተከሽኖ
በዕንቁጣጣሽ ሰብል ታጥኖ
ኢዮሃ አበባዬ ሆኖ፥
ጨረቃዋ ከቆባዋ፥ ከሽልምልሚት እምቡጧ
ጧ ብላ ከሰንኮፈንዋ፥ ተንዠርግጎ የእንኮይ ቡጧ፥
ድንግል ጽጌ-ረዳ ፈልቃ
ፍልቅልቂት ድምቡል ቦቃ …
ተንሠራፍታ የአበባ ጮርቃ፥
ታድያን ብሌኑ የጠጠረ
ባሕረ-ሃሳቡ የከረረ
የውበት ዓይኑ የታወረ
ልበ-ሕሊናው የሰለለ
አይ፥ አበባ አይደለም አለ፤
አይ፥ እሳት አይደለም አለ፤
ያልታደለ። …
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ፥ እሳት አደል ብሎ ካደ
እቶን ባይኑ እየነደደ።
ከዋክብቱ እንደ ችቦ
በነበልባል ወርቀ ዘቦ
ከፅንፍ ፅንፍ አውለብልቦ
ደመራው እየተመመ
እየፋመ እየጋመ
ደመና እንደንዳድ ሲነድ
መንጸባርቅ ሰደድ ሲወርድ፥
በራሪ ኮከብ ተኩሶ
በአድማሳት እሳት ለኩሶ…
ይኸ እንደኔና እንዳንቺው፥ የውበት ዓይኑ የሰለለ
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ፥ እሳት እኮ አይደለም አለ፥
ያልታደለ። …
… ይቅር ብቻ አንናገርም፥
እኔና አንቺ አንወያይም፤
ለውይይት አልታደልንም
እንዲያው ዝም፥ እንዲያው ዝም … ዝም።
አበባ አንሆን ወይ እሳት
ተጠምደን በምኞት ቅጣት
ሰመመን ባጫረው መዓት
ዕድሜአችንን እንዳማጥናት፤ …
እሳት አንሆን ወይ አበባ
በሕቅ እንቅ ስንባባ
ባከነች ልጅነታችን፥ እየቃተትን ስናነባ
ሳንፈጠር በሞትንባት
ሳናብብ በረገፍንባት
ሳንጠና ባረጀንባት
አበባ ወይንም እሳት፥ መሆኑን ብቻ አጣንባት።
“— እሳት ወይ አበባ | ከጸጋዬ ገብረ መድኅን | 1960/1999 ዓ.ም ታተመ | ገጽ 152-154

ምንም አስተያየቶች የሉም:
አስተያየት ይለጥፉ